ሶላትን በተመለከተ ጥርጣሬ በሁለት ይከፈላል ፡-
1 - ሶላቱ ካበቃ በኋላ የሚሆን ጥርጣሬ
ለዚህ ዓይነቱ ጥርጣሬ ትኩረት አይሰጥም፡፡
ምሣሌው ፡- አንድ ሰው ከፈጅር ሶላት በኋላ ሁለት ረክዓ ነው ወይስ ሦስት ነው? ብሎ መጠራጠር ነው፡፡ እርግጠኛ ሆኖ በተረጋገጠለት ነገር ከመስራት ውጭ ለዚህ ጥርጣሬ ግምት አይሰጥም፡፡
2 - ሶላቱ ውስጥ እያሉ የሚፈጠር ጥርጣሬ
ይህ ጥርጣሬ ከሁለት ሁኔታዎች አንዱ ነው ፡-
ሀ- ከሁለት ነገሮች ውስጥ አንዱን አመዛኝ ሆኖ ማግኘት
በዚህ ሁኔታ አመዛኝ ሆኖ በተገኘው መሰረት በመፈጸም ከሰላምታ በኋላ የማካካሻ ሱጁድ ይወርዳል፡፡
ምሣሌው ፡- አንድ ሰጋጅ ዙህር በመስገድ ላይ እያለ ሁለተኛው ረክዓ ነው ወይስ ሦስተኛው ነው? ብሎ ተጠራጥሮ ሦስት ነው የሚለውን አመዛኝ ሆኖ አገኘው፡፡ በዚህ ሁኔታ ሦስት ነው ብሎ ሶላቱን ያሟላና ከሰላምታ በኋላ የማካካሻ ሱጁድ ይወርዳል፡፡
ለዚህ ማስረጃው የሚከተለው የነቢዩ ﷺ ቃል ነው ፡- ‹‹አንዳችሁ በሶላቱ ከተጠራጠረ ትክክለኛውን ለማወቅ ጥረት ያድርግ፤ከዚያም ሰላምታ ይበልና ሁለት ሱጁድ ይውረድ፡፡›› [በእብን ሒባን የተዘገበ]
ሰላምታ ይላል የመርሳት ሱጁድ ይወርዳል
ለ- ከሁለት አንዱም አመዛኝ ሆኖ አለመገኘት
በዚህ ሁኔታ በአነስተኛው ቁጥር ላይ ተሞርክዞ ሶላቱን በማጠናቀቅ የመርሳት ሱጁድ ይወርዳል፡፡
ምሣሌው ፡- አንድ ሰጋጅ ዙህር በመስገድ ላይ እያለ ሁለተኛው ረክዓ ነው ወይስ ሦስተኛው ነው ብሎ ተጠራጥሮ ሁለቱም አመዛኝ ሳይሆኑ ይቀራሉ፡፡ በዚህ ሁኔታ በአነስተኛው ቁጥር ላይ ተመስርቶ ሶላቱን ያሟላና ከሰላምታ በፊት የማካካሻ ሱጁድ ይወርዳል፡፡
ለዚህ ማስረጃው የሚከተለው የነቢዩ ﷺ ቃል ነው፡- ‹‹አንዳችሁ በሶላቱ ከተጠራጠረና ሶስት ይሆን አራት ስንት እንደ ሰገደ ካላወቀ፣ጥርጣሬውን ወደ ጎን ያድርግ፣አመዛኝ ሆኖ ባገኘው ላይ ይመስርት፤ከዚያ ከሰላምታ በፊት ሁለት ሱጁድ ያድርግ፡፡›› [በሙስሊም የተዘገበ]
የመርሳት ሱጁድ ይወርዳል ሰላምታ ይላል
2 - ጭማሬ
ይህ ሰጋጁ በሶላቱ ውስጥ ሩኩዕ ወይም ሱጁድ፣ . . ወዘተ. የመጨመር ሁኔታ ነው፡፡ ጭማሬው ከሚከተሉት ሁለት ሁኔታዎች አንዱ ከመሆን አያልፍም ፡-
ሀ- ሰጋጁ በማድረግ ላይ እያለ ጭማሪውን የሚያስታውስበት ሁኔታ፡፡
ይህ ከሆነ ከድርጊቱ መታቀብ ግዴታ ይሆንበታል፡፡ ከዚያ ሶላቱን ያሟላና ከሰላምታ በኋላ የማካካሻ ሱጁድ ይወርዳል፡፡
ምሣሌው ፡- አንድ ሰጋጅ ዙህር በመስገድ ላይ እያለ አምስተኛ ረክዓ ለመስገድ ተነስቶ ከቆመ በኋላ ጭማሪ መሆኑን ያስታውሳል፡፡ በዚህ ሁኔታ ወዲያውኑ ተመልሶ በመቀመጥ ሶላቱን ማጠናቀቅ ይኖርበታል፡፡ ከሰላምታ በኋላ የመርሳት ሱጁድ ይወርዳል፡፡
ለ- ሰጋጁ በመጨመር ላይ እያለ ጭማሪውን የሚያስታውስበት ሁኔታ፡፡
በዚህ ሁኔታ ሶላቱን ያሟላና ከሰላምታ በኋላ የማካካሻ ሱጁድ ያደርጋል፡፡ ለዚህ ማስረጃው ከእብን መስዑድ (ረዐ) የተላለፈው የሚከተለው ሐዲስ ነው ፡- ‹‹ነቢዩ ﷺ ዙህርን አምስት ረክዓ ሰገዱና ‹በሶላቱ ጭማሬ ተደረገ ወይ?› ተብለው ተጠየቁ፡፡ ምን ተደረገ? ሲሉ ‹‹አምስት ነው የሰገዱት›› ተባሉና ከሰላምታ በኋላ ሁለት ሱጁድ ወረዱ፡፡›› [በቡኻሪ የተዘገበ]
3 - ጉድለት
ይህ ሰጋጁ ከሶላት ማእዘናት ወይም ከግዴታዎቹ አንዱን ማእዘን ወይም አንዱን ግዴታ የማጓደል ሁኔታ ነው፡፡
1 - የማእዘን ጉድለት
ይህ ማእዘን የእሕራም ተክቢራ ከሆነ ሶላቱ ውድቅ ነው፣ሶላቱ ከነአካቴው አልተመሰረተምና፡፡ ጉድለቱ ከእሕራም ተክቢራ ውጭ ካሉት ማእዘናት አንዱ ከሆነ ሁኔታው ከሚከተሉት ሁለት ሁኔታዎች አንዱ ከመሆን አይዘልም ፡-
ሀ- ሰጋጁ በቀጣዩ ረክዓ ላይ በተረሳው ማእዘን ላይ ከደረሰ በኋላ ያስታወሰ መሆን፡፡
ሁኔታው ይህ ከሆነ ማእዘኑ የጎደለበትን ረክዓ ውድቅ አድርጎ በቀጣዩ ረክዓ ይተከዋል፡፡
ምሣሌው ፡- አንድ ሰጋጅ በመጀመሪያው ረክዓ ሩኩዕ ረስቶ በሁለተኛው ረክዓ ሩኩዕ ላይ መርሳቱን ያስታውሳል፡፡ በዚህ ሁኔታ አሁን ያለበትን ረክዓ የመጀመሪያው ረክዓ አድርጎ በመውሰድ የበፊተኛውን ረክዓ ውድቅ አድርጎ ሶላቱን ያሟላል፤ከሰላምታ በኋላ የማካካሻ ሱጁድ ይወርዳል፡፡
ሰላምታ ይላል የመርሳት ሱጁድ ይወርዳል
ለ- ሰጋጁ በቀጣዩ ረክዓ ላይ በተረሳው ማእዘን ላይ ከመድረሱ በፊት ያስታወሰ መሆን፡፡
እዚህ ላይ ወደ ተተወው ማእዘን ተመልሶ በማከናወን ሶላቱን ያሟላና ከሰላምታ በኋላ የመርሳት ሱጁድ ይወርዳል፡፡
ምሣሌው ፡- በመጀመሪያው ረክዓ ላይ ሁለተኛውን ሱጁድና ከርሱ በፊት ያለውን መቀመጥ ረስቶ ከሁለተኛው ረክዓ ሩኩዕ ቀና ካለ በኋላ ያስታወሰ ሰው ነው፡፡ በዚህ ሁኔታ ተመልሶ በመቀመጥ ሱጁድ ይወርድና ሶላቱን በማሟላት ከሰላምታ በኋላ የማካካሻ ሱጁድ ይወርዳል፡፡
2 - የዋጅብ ጉድለት
አንድ ሰጋጅ ከሶላት ዋጅቦች ውስጥ አንዱን ዋጅብ ከረሳ ሁኔታው ከሚከተሉት ሦስት ሁኔታዎች አንዱ ከመሆን አያልፍም ፡-
ሀ- የተረሳውን ዋጅብ ቦታ ለቆ ወደ ሌላ ሳይተላለፍ ያስታወሰው መሆን፡፡
በዚህ ሁኔታ ዋጅቡን መፈጸም ነው፤ሌላ ነገር አይኖርበትም፡፡
ለ- ሰጋጁ በሶላቱ ውስጥ የተረሳውን ዋጅብ ቦታ ለቆ ወደ ሌላ ከተላለፈ በኋላ ወደ ቀጣዩ ማእዘን ከመድረሱ በፊት ያስታወሰው መሆን፡፡
በዚህ ሁኔታ ወደ ተወው ተመልሶ በመፈጸም ሶላቱን ያሟላና ከሰላምታ በኋላ የመርሳት ሱጁድ ይወርዳል፡፡
ሐ- ወደ ቀጣዩ ማእዘን ከደረሰ በኋላ ያስታወሰው መሆን፡፡
እዚህ ላይ ሶላቱን ይቀጥላል፤ወደዚያ ተመልሶ አይሄድም፡፡ ከሰላምታ በፊት የማካካሻ ሱጁድ ይወርዳል፡፡
ምሣሌው ፡- በሁለተኛው ረክዓ ከሁለተኛው ሱጁድ ተሸሁድን ረስቶ ለሦስተኛው ረክዓ ተነስቶ ቀጥ ብሎ ከመቆሙ በፊት መርሳቱን ያስታወሰ ሰጋጅ ነው፡፡ ይህ ለተሸሁድ ተቀምጦ ሶላቱን ያሟላል፣ማካካሻ የለበትም፡፡
ተነስቶ ከቆመ በኋላና ቀጥ ብሎ ሙሉ በሙሉ ከመረጋጋቱ በፊት ካስታወሰ ለተሸሁድ ተመልሶ ይቀመጥና ሶላቱን ያሟላል፤ ከሰላምታ በኋላ የማካካሻ ሱጁድ ይወርዳል፡፡ ሙሉ በሙሉ ተረጋግቶ ከቆመ በኋላ ካስታወሰ ግን ተመልሶ አይቀመጥም፡፡ ሶላቱን ያሟላና ከሰላምታ በፊት የመርሳት ሱጁድ ይወርዳል፡፡
ለዚህ ማስረጃው ከዐብዱላህ ብን ቡሐይና (ረዐ) የተላለፈው የሚከተለው ሐዲስ ነው ፡- ‹‹ነቢዩ ﷺ ዙህርን አሰገዷቸውና በመጀመሪያዎቹ ሁለት ረክዓዎች ሳይቀመጡ ተነስተው ቆሙ፤ሰውም አብሯቸው ተነስቶ ቆመ፡፡ ሶላቱ ሲያበቃ ሰው ሰላምታ ይላሉ ብሎ ሲጠብቅ አል’ሏሁ አክበር ብለው ሁለት ሱጁድ ወረዱና ሰላምታ አሉ፡፡›› [በቡኻሪ የተዘገበ]
ካለፈው የምንረዳው የመርሳት ሱጁድ ከሰላምታ በፊትና ከሰላምታ በኋላም የሚደረግ መሆኑን ነው፡፡
የመርሳት ሱጁድ አደራረግ
የመርሳት ሱጁድ (ሱጁድ አስ’ሰህው) ከመደበኛው የሶላት ሱጁድ ጋር አንድ ነው፡ ሲወርዱና ቀና ሲሉም ተክቢራ ይደረግበታል፡ በሱጁዱ ውስጥና በሁለቱ ሱጁዶች መካከከል የሚደረገው ዝክርም አንድ ዓይነት ነው፡፡
ጠቃሚ ነጥቦች
1 - አንድ ሰጋጅ ሶላቱን ከማሟላቱ በፊት ሰላምታ ካለና አለማሟላቱን ከረዥም ጊዜ በኋላ እንጂ ያላስታወሰው ከሆነ ሶላቱን እንደ አዲስ ዳግም ይሰግዳል፡፡ በአጭር ጊዜ ውስጥ ከሁለትና ሦስት ደቂቃ ባልበለጠ ጊዜ ውስጥ ካስታወሰ ሶላቱን ያሟላና የማካካሻ ሱጁድ ይወርዳል፡፡
2 - መእሙም ኢማሙ ከረሳበት ቦታ በኋላ ከጀማዓው የተቀላቀለ ቢሆን እንኳ በመርሳት ሱጁድ ኢማሙን መከተል ይኖርበታል፡፡
3 - አንድ ሰጋጅ ሁለት ዝንጋታዎች (ሰህው) ኖሮበት አንደኛው ከሰላምታ በፊት ሀለተኛው ደግሞ ከሰላምታ በኋላ ሱጁድ የሚወረድበት ከሆነ ከሰላምታ በፊት በሚያደርገው የመርሳት ሱጁድ ብቻ ይወሰናል፡፡
የእሕራም ተክቢራ የመርሳት ሱጁድ
ሁለተኛ - የምስጋና (የሹክር) ሱጁድ